
በርክክብ መርሃ ግብሩ ላይ ንግግር ያደረጉት የጤና ሚኒስትር ዶ/ር መቅደስ ዳባ ይህ ተነሳሽነት በጤና ተቋማት ውስጥ አስተማማኝ የኃይል አቅርቦትን በከፍተኛ ሁኔታ እንደሚያሰፋ ተናግረዋል። 380 የጤና ተቋማት የፀሐይ ኤሌክትሪክ ሃይል አገልግሎት ያገኛሉ፤ ይህም ያልተቋረጡ አገልግሎቶችን ለማረጋገጥ ይረዳቸዋል ብለዋል። ሚኒስትሯ በተጨማሪም 1,183 በሃገር ውስጥ የተገጣጠሙ ሞተር ሳይክሎች ለመድረስ አስቸጋሪ በሆኑ አካባቢዎች ክትባቶችን እና መድሃኒቶችን ለማድረስ እንደሚደግፉ አፅንኦት ሰጥተዋል።
ዶ/ር መቅደስ መንግስት ለአየር ንብረት ተፅዕኖ የማይበገር የጤና ተቋማትን ለመገንባት እየሰራ መሆኑን ገልጸዋል፤ እንዲሁም ሚኒስቴሩ የኢትዮጵያን የጤና ስርዓት ለማጠናከር ከልማት አጋሮች ጋር በመተባበር መስራቱን እንደሚቀጥል ያለውን ቁርጠኝነት አረጋግጠው፤ ድጋፍ ላደረጉ አካላት ምስጋና አቅርበዋል።
የጤና ሚኒስትር ዴኤታ ዶ/ር ደረጄ ዱጉማ ፕሮጀክቱ በተለይም በገጠር አካባቢዎች በጤና አገልግሎት አሰጣጥ ላይ ያሉ የፍትሃዊነት ክፍተቶችን ለመፍታት ይረዳል ብለዋል። ታዳሽ እና ዘላቂ የኃይል መፍትሄዎችን መጠቀም የጤና ዘርፉን ለማጠናከር እና የእናቶች እና የህፃናት ጤና አገልግሎቶችን ለማሻሻል አስፈላጊ መሆኑን አክለዋል። የክልል የጤና ቢሮዎች የተበረከቱትን መሳሪያዎች በአግባቡ እንዲጠቀሙ እና እንዲጠብቁ ጥሪ አቅርበዋል።
የዩኒሴፍ የኢትዮጵያ የሀገር ውስጥ ተወካይ ዶ/ር አቡባካር ካምፖ ርክክቡ አገሪቱ የጤና አገልግሎቶችን ለማሻሻል እና በጤና ተቋማት ውስጥ አስተማማኝ የኃይል አቅርቦትን ለማስፋፋት ያላትን ቁርጠኝነት ያሳያል። ኢትዮጵያ በጤና ዘርፉ ውስጥ የታዳሽ የኃይል መፍትሄዎችን በመተግበር ረገድ አስፈላጊ እርምጃዎችን እየወሰደች መሆኑን ተናግረዋል።
የውሃ እና የኢነርጂ ሚኒስትር ዴኤታ ዶ/ር ኢ/ር ሱልጣን ዋሊ የአገሪቱን ሰፊ የታዳሽ የኃይል አቅም አጉልተው ገልጸው፤ መንግስት ከኃይል ማመንጫ ውጭ በሚታደሱ የኃይል ስርዓቶች አማካኝነት የሀገር ውስጥ የኃይል ፍላጎትን ለማሟላት አቅዷል ብለዋል። የጤና ተቋማት የፀሐይ ኃይል ኤሌክትሪክ ፕሮጀክት ከኢትዮጵያ ሰፊ የልማት አጀንዳ ጋር የሚጣጣም መሆኑን አክለዋል።
የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የማህበራዊ፣ የባህልና የስፖርት ቋሚ ኮሚቴ ሊቀመንበር ወርቅሰሙ ማሞ ጤና ሚኒስቴር የእናቶችና የህፃናት ጤና አገልግሎቶችን ለማሻሻል ላሳየው ቁርጠኝነት ምስጋና አቅርበዋል። ሚኒስቴሩ የእናቶችና የህፃናት ሞትን በመቀነስ ረገድ ላከናወናቸው ስኬቶች እውቅና ሰጥተዋል።
በሥነ ሥርዓቱ ላይ የጤና ሚኒስትር ዶ/ር መቅደስ ዳባ የፀሐይ ኤሌክትሪክ ሃይል ማመንጫዎችን እና ሞተር ሳይክሎችን ለክልል ጤና ቢሮዎች በይፋ አስረክበዋል።
Website: moh.gov.et
Facebook: Ministry of Health,Ethiopia
Twitter: x.com/fmohealth
YouTube: youtube.com/@FMoHealthEthiopia
Tiktok: tiktok.com/@mohethiopia
Telegram: t.me/M0H_EThiopia
Linkedin: lnkd.in/ewFJ6VAB



