
በጤና ሚኒስቴር የመድኃኒት፣ ህክምና መሳሪያዎች እና መገልገያዎች መሪ ስራ አስፈፃሚ ከኢትዮጵያ መድኃኒት አቅራቢ አገልግሎት ጋር በመሆን በሀገር አቀፍ ደረጀ ያለውን የግብዓት አቅርቦት አፈፃፀም ከሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ጋር በመሆን ገምግሟል።
የኢትዮጵያ መድኃኒት አቅራቢ አገልግሎት የፍላጎት አስተዳደር ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ ወርቅነህ አበበ የክትባት አቅርቦቱ ስኬታማ እንዲሆን አጋር ድርጅቶች እና ባለድርሻ አካላት ከፍተኛ አስተዋፆ እንዳላቸው ገልፀው፣ ወደ 22 ሚሊዮን የሚሆኑ ህፃናትን በያዝነው በጀት ዓመት መከተብ እንደተቻለም ተናግረዋል።
በጤና ሚኒስቴር በእናቶች፣ ህፃናት አፍላ ወጣቶች ጤና አገልግሎት መሪ ስራ አስፈፃሚ የክትባት አገልግሎት ዴስክ ኃላፊ አቶ መልካሙ አያሌው በበኩላቸው የተቀናጀ የክትባት አቅርቦት ሰንሰለት ስርዓቱን ማጠናከር በሀገር አቀፍ ደረጃ ላለው የክትባት ፕሮግራም ስኬት የጀርባ አጥንት መሆኑን ገልፀዋል።
የመጀመሪያውን ዙር የፀረ አምስት ክትባት(Pentavalent 1) የተከተቡ ህፃናት ሽፋን እ.ኤ.አ በ2020 ከነበረበት 71 በመቶ በ 2024 ወደ 81 በመቶ ከፍ ማለቱን አቶ መልካሙ ጠቁመው ይሁን እንጂ በርካታ ህጻናት ክትባቱን ያልጀመሩ ወይም ጀምረው ያቋረጡ መኖራቸውን በመግለፅ ክትባቱን ያልጀመሩ ከ5 ዓመት በታች ያሉ ህጻናት ወደ ጤና ተቋም በመሄድ የማካካሻ ክትባት መውሰድ እንደሚገባቸው በመድረኩ ተነስቷል።
Website: moh.gov.et
Facebook: Ministry of Health,Ethiopia
Twitter: x.com/fmohealth
YouTube: youtube.com/@FMoHealthEthiopia
Tiktok: tiktok.com/@mohethiopia
Telegram: t.me/M0H_EThiopia
Linkedin: lnkd.in/ewFJ6VAB
