
በሚቀጥሉት 10 ቀናት በአብዛኛው የሀገሪቱ ክፍል የሚኖረውን የበጋ ደረቅ ርጥበት በመጠቀም አርሶ አደሮች ሰብል የመውቃትና ምርት የማጓጓዝ ስራ እንዲያከናውኑ የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት አሳሰበ።
ኢንስቲትዩት ለኢዜአ በላከው የትንብያ መግለጫ እንደጠቆመው በቀጣይ 10 ቀናት በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች ደረቅ፣ ፀሐያማና ነፋሻማ የአየር ፀባይ ሁኔታ ተጠናክሮ ይቀጥላል።
በሰሜን፣ በምሥራቅ፣ በሰሜን ምሥራቅና በደቡብ ደጋማ የሀገሪቱ አካባቢዎች በሌሊትና በማለዳ ቅዝቃዜ እንደሚኖር ገልጿል።
በዚህም በአብዛኛው የሀገሪቱ ክፍል የሚኖረውን የበጋ ደረቅ ርጥበት በመጠቀም አርሶ አደሮች በመኸር ወቅት የሰበሰቧቸውን ሰብሎች በወቅቱ የመውቃት እና ምርቶችን የማጓጓዝ ስራዎችን እንዲያከናውኑ መክሯል።
የበልግ ወቅት በመቃረቡም የሰብል ማሳዎችን ከማንኛውም ተረፈ ምርት ነጻ የማድረግና ዘር የማዘጋጀት ስራዎችን ሊሰሩ እንደሚገባም ጠቁሟል።
ጥር ወር ወደ በልግ ወቅት መሸጋገሪያ በመሆኑም የሚኖረውን መጠነኛ ርጥበት ለውሀ ሀብት መሻሻል አቅም መጠቀም ይገባልም ብሏል።
የአፋር ደናክል፣ ዋቢ ሸበሌ፣ ገናሌ ዳዋ ፣ መረብ ጋሽ፣ ኦጋዴን፣ አይሻ፣ ባሮ አኮቦ፣ አባይ እና የተከዜ ተፋሰሶች ደረቅ የአየር ጸባይ ሁኔታን እንደሚያስተናግዱ ተጠቁሟል።
ነገር ግን በወሩ መጨረሻ ጥቂት ቀናት በላይኛውና በመካከለኛው ስምጥ ሸለቆ እና በተወሰኑ የላይኛው ኦሞ ጊቤ እና አዋሽ ተፋሰሶች ላይ መጠነኛ ርጥበት የሚያገኙ ይሆናል።
ለሌሎች መረጃ